A

Addis

ዜና

November 06, 2024

መንግሥት ያለበትን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዕዳ ለመክፈል የ845 ቢሊዮን ብር ቦንድ አፀደቀ

Politic

By

ሲሳይ ሳህሉ

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለዓመታት እያበደረ ሳይመለስለት የቀረና ከእነ ወለዱ የተጠራቀመ ከ845 ቢሊዮን ብር በላይ ለመክፈል፣ መንግሥት የቦንድ ሽያጭ እንዲፈጽም የሚፈቅድለት አዋጅ በፓርላማው ፀደቀ፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማክሰኞ ጥቅምት 26 ቀን 2017 ዓ.ም. ባካሄደው 4ኛ ዓመት ይፋ የሥራ ዘመኑ፣ የመንግሥት ዕዳ ሰነድ ረቂቅ የተሰኝ አዋጅ መርምሮ በአንድ ንባብ አፅድቋል፡፡

በአዋጁ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የወሰዱትን ብድር ለመክፈል ባለመቻላቸው ዕዳውን መንግሥት ተረክቦ፣ የዕዳው ክፍያ በመንግሥት ዕዳ ሰነድ ወይም ቦንድ እንዲከፈል ማድረግ አስፈላጊ መሆኑ ተጠቅሷል፡፡

በምክር ቤቱ በአብላጨ ድምፅ የፀደቀው አዋጅ ላይ እንደተመላከተው የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ለሜጋ ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ ከወሰዱት ብድር ውስጥ ከፍተኛውን መጠን የሚይዘው፣ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የተወሰደው ብድር መሆኑ ተገልጿል፡፡

ይሁን እንጂ ሜጋ ፕሮጀክቶች ከጥናት ጀምሮ በርካታ የተወሳሰበ ችግር ያለባቸው በመሆኑ፣ የውጭ አገርም ሆነ የአገር ውስጥ ዕዳቸውን ለመክፈል ከማይችሉበት ደረጃ ላይ መድረሳቸው ተብራርቷል፡፡

መንግሥት የልማት ድርጅቶቹ በዕዳ ጫና ምክንያት ያጋጠማቸውን ችግር በማቃለል አትራፊ ሆነው ሥራቸውን መቀጠል እንዲችሉ፣ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የወሰዱትን ብድር ተረክቦ ከተለያዩ ምንጮች በሚያገኘው ገቢ ዕዳውን የሚከፍል የዕዳና የሀብት አስተዳደር ኮርፖሬሽን ከጥቂት ዓመታት በፊት ማቋቋሙ ይታወሳል፡፡

የዕዳና የሀብት አስተዳደር ኮርፖሬሽን በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ በ570 ቢሊዮን ብር የተፈቀደ ካፒታል፣ እንዲሁም በ142 ቢሊዮን ብር የተከፈለ ካፒታል የተቋቋመ የመንግሥት የልማት ድርጅት ሲሆን፣ ከኢንዱስትሪ ልማት ፈንድ የሚመደብለትን ካፒታልና ከንግድ ሥራ እንቅስቃሴ የሚያገኘውን ገቢ፣ በተጨማሪም ከሌሎች ምንጮች የሚመደብለትን ገንዘብ በመጠቀም ዕዳውን ለመክፈል የተቋቋመ የመንግሥት የልማት ድርጅት ነው።

ይሁን እንጂ በአዋጁ እንደተብራራው መንግሥት በኮርፖሬሽኑ ማቋቋሚያ ደንብ ከተመለከተው የተከፈለ ካፒታል ውስጥ ሊያሟላ የቻለው 44 ቢሊዮን ብር ብቻ ሲሆን፣ ቀሪውን ብር 100 ቢሊዮን ብርና በጥቅሉ ሲታይ የተፈቀደውን የኮርፖሬሽኑን ካፒታል  570 ቢሊዮን ብር ሊያሟላ እንዳልቻለ ተገልጿል፡፡

በዚህም ያልተከፈለው ከፍተኛ ዕዳ ብድሩን ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች በሰጠው በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የፋይናንስ ገጽታ ላይ አሉታዊ ውጤትን ማስከተሉ ተብራርቷል፡፡

የዕዳና የሀብት አስተዳደር ኮርፖሬሽን በሁለት ዙር የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የወሰዱትን ብድር ከእነ ወለዱ መረከቡ በሰነዱ ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች አበድሮ ካልተመለሰለት አጠቃላይ ዕዳው ውስጥ በመጀመሪያ ዙር ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ብድር 3.25 ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም ወለድ ብር 120 ሚሊዮን በአጠቃላይ 3.369 ቢሊዮን ብር፣ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን ዋና ብድር 92.3 ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም ወለዱ 9.3 ቢሊዮን ብር፣ በድምሩ 101.7 ቢሊዮን ብር፣ የኢትዮ ኢንጂነሪንግ ግሩፕ ዋና ብድር  11.478 ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም ወለዱ 4.9 ቢሊዮን ብር በድምሩ 16.4 ቢሊዮን ብር መሆኑ ተገልጿል፡፡ በተጨማሪም በሁለተኛው ዙር አበድሮ ካልተመለሰለት ውስጥ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ዋና ብድር ብር 179.2 ቢሊዮን፣ እንዲሁም ወለድ 12.5 ቢሊዮን ብር በድምሩ 191.7 ቢሊዮን ብር፣ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ብድር  68.6 ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም ወለድ 4.205 ቢሊዮን ብር፣ በድምሩ 72.8 ቢሊዮን ብር በአጠቃላይ ስድስት የልማት ድርጅቶች ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የተበደሩትን ዋና ብድር 365.2 ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም የተጠራቀመ ወለድ ብር 33.4 ቢሊዮን በድምሩ ብር 398.6 ቢሊዮን ብር ዕዳ ይገኝበታል፡፡

በተጨማሪም በተፈረሙ የዕዳ ማስተላለፊያ ስምምነቶች የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች ያበደራቸውና ተመልሰው ያልተከፈሉ ዕዳዎች ውስጥ የስኳር ኮርፖሬሽን ዋና ብድር 3 ቢሊዮን ብር ወለዱ 5.9 ቢሊዮን ብር፣ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ብድር 3 ቢሊዮን ብር ወለዱ 4.3 ቢሊዮን ብር፣ የኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ግሩፕ ዋና ብድር 5.2 ቢሊዮን ብር ወለዱ 1 ቢሊዮን ብር፣ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራዎች ዋና ብድር 1.4 ቢሊዮን ብር ወለዱ 4 ቢሊዮን ብር ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአገሪቱ ንግድ ባንክ እንቅስቃሴ ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የያዘ ቢሆንም፣ የተፈቀደለት ካፒታል አራት ቢሊዮን ብር ብቻ መሆኑ በአዋጁ ተመላክቷል፡፡

ባንኩ በገበያው ውስጥ ያለውን ድርሻ ይዞ እንዲቀጥል ለማድረግ ደረጃ በደረጃ የተከፈለውን ካፒታል ማሳደግ አስፈላጊ በመሆኑ ያልተመለሰለትን ዕዳ በ845 ቢሊዮን ብር ዕዳ መክፈያ ሰነድ እንዲከፈለው ከማድረግ በተጨማሪ፣ የባንኩን ካፒታል ለማሳደግ የሚውል የ54 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ ቦንድ እንደሚኖር ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች በብድር የሰጠው ገንዘብ ወደ ኮርፖሬሽኑ ሲተላለፍ ለዕዳው መክፈያ ከኢንዱስትሪ ልማት ፈንድ የሚመደብለትን ካፒታል፣ ከንግድ ሥራ እንቅስቃሴ የሚያገኘውን ገቢ፣ እንዲሁም ከሌሎች ምንጮች የሚመደብለትን ገንዘብ ይጠቀማል በሚል ዕሳቤ ቢሆንም ባንኩ በታቀደው መሠረት ዕዳውን ለመክፈል የሚያስችል በቂ የገቢ ምንጭ ሊያገኝ አለመቻሉ በአዋጁ ተገልጿል፡፡

መንግሥት ከሦስት ዓመታት የችሮታ ጊዜ በኋላ በ10 ዓመታት ውስጥ  የመንግሥት ቦንድ ዕዳውን ቢከፍል፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን የፋይናንስ ገጽታ በመጠበቅ ረገድ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተጠቅሷል፡፡

የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ውስጥ አብዛኞቹ በሒደት ወደ ግል ባለቤትነት የሚዘዋወሩ በመሆናቸው፣ ከሽያጫቸው የሚገኘውን ገቢና ከሌሎችም የመንግሥት የገቢ ምንጮች ወደ ቦንድ የተቀየረውን ዕዳ መክፈል እንደሚቻል በፀደቀው አዋጅ ተብራርቷል፡፡

Comments

No comments yet. Be the first to leave a comment!

Leave a Comment

Related Posts

Subscribe

You must accept the terms to subscribe.

© Copyright 2025 Addis News. All rights reserved.