October 23, 2024
ምሕረት ሞገስ
ሃማስ ከጋዛ ወደ እስራኤል በተኮሳቸው ከሦስት ሺሕ የሚልቁ ሮኬቶች የተጀመረው የእስራኤል ጋዛ ፍልስጤም ጦርነት፣ ዛሬ ላይ አድማሱን አስፍቶ ወደ ሊባኖስ ሂዝቦላህ ብሎም ሶሪያ ደርሷል፡፡
ከሮኬቶች ጥቃት፣ ከእግረኛ ጦርነት፣ ከተዋጊ ጀቶች የቦንብ ውርጅብኝ አልፎም አሁን ላይ በእስራኤልና አሜሪካ ውስጥ አይደፈሬ የተባለ ሚስጥር እስከመሹለክ ተወሳስቧል፡፡
እ.ኤ.አ. በጥቅምት 2023 በእስራኤልና ሃማስ መካከል ለተጀመረው ጦርነትና አጠቃላይ ለመካከለኛው ምሥራቅ ሰላም መደፍረስ ከኋላ ኢራን አለች የምትለው እስራኤል፣ በቀጣይ ኢራን ላይ ዕርምጃ ለመውሰድ ስለማቀዷ የተሰናዳው ሰነድ አፈትልኮ መውጣቱን የዋይት ሐውስ ብሔራዊ ደኅንነት ካውንስል ቃል አቀባይ ጆን ኪርባይ ተናግረዋል፡፡
ሰነዱ የወጣው ተጠልፎ ይሁን አፈትልኮ ግልጽ ያላደረጉት ቃል አቀባዩ፣ ሰነዱ እስራኤል ኢራን ከሁለት ሳምንታት በፊት ለሰነዘረችባት የሚሳይል ጥቃት አፀፋ ለመስጠት ስለምታደርገው ወታደራዊ ዝግጅት ዕቅድና የአሜሪካን ዳሰሳ ያካተተም ነበር፡፡
ጥብቅ ሚስጥር ተብሎ የተዘጋጀው ሰነድ የአሜሪካ፣ የእንግሊዝ፣ የካናዳ፣ የኒውዚላንድና የአውስትራሊያ ጥምር ለሆነው ደኅንነት ክፍል የተላከም ነበር፡፡
ይህንኑ ተከትሎ ለሚሰነዘርባት ጥቃት ምላሽ እንደምትሰጥ ኢራን ስታስታውቅ፣ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ደግሞ ትናንት ጥቅምት 12 ቀን 2017 ዓ.ም. ከእስራኤል ባለሥልጣናት ጋር ለመምከር ቴልአቪቭ ገብተዋል፡፡
እስራኤል በኢራን ላይ ወታደራዊ ዕርምጃ የመውሰዷ ሁኔታ ባየለበትና የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረስ የተደረጉ ጥረቶች ሁሉ ይሁንታ ባጡበት የብሊንከን ቴልአቪብ መግባት፣ በመካከለኛው ምሥራቅ እየተስፋፋ የመጣውን ጦርነት ለማስቆም የተጀመረውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ለማጠናከር እንደሆነ ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡
እስራኤልና ሃማስ ከዓመት በፊት የጀመሩትን ጦርነት በአንድ ወገን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ፣ በሌላ በኩል ለእስራኤል የጦርና የገንዘብ ድጋፍ በማድረግ የምትሳተፈው አሜሪካ፣ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሯን ወደ እስራኤል ስትልክ የአሁኑ ለ11ኛ ጊዜ ነው፡፡
የአሁኑ የብሊንከን ጉዞ በተለይ እስራኤል በኢራን ላይ ወታደራዊ ዕርምጃ ለመውሰድ ማቀዷ አፈትልኮ ከወጣበትና እስራኤል በሊባኖስና በጋዛ ፍልስጤም እየወሰደች ያለው ወታደራዊ ዕርምጃ ባየለበት ነው፡፡
እስራኤል በሊባኖስና በጋዛ የምታደርገው ወታደራዊ ዕርምጃ ቢያይልም፣ በእስራኤል ላይ የሚሰነዘሩ ጥቃቶችም እየጨመሩ ነው፡፡ ብሊንከን ቴልአቪቭ ከመድረሳቸው ሰዓታት አስቀድሞም ሂዝቦላህ ወደ ከተማዋ ሮኬት መተኮሱ ተሰምቷል፡፡ እስራኤላውያን የፍንዳታ ድምጾች መስማታቸውን ሲገልጹ፣ መንግስት ደግሞ ‹‹ብዙዎቹን አክሽፌያለሁ፣ የቀሩትም ባዶ ስፍራ ላይ አርፈዋል›› ብሏል፡፡
እስራኤል ከፍልስጤም ጋዛ የገጠመችው ጦርነት ሳያባራ በሊባኖስ ሂዝቦላህ ላይ የጀመረችው ጦርነት በሊባኖስ ብቻ የሚያቆም ሳይሆን፣ የሂዝቦላህ አባላት ይገኙባቸዋል በሚባሉ የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች በሙሉ እንደሚሆን የእስራኤል መከላከያ ሚኒስቴርን ጠቅሶ ኤቢሲ ዘግቧል፡፡
እስራኤል በሂዝቦላህና ሃማስ ላይ በምትወስደው ዕርምጃ ሆስፒታሎችን ጨምሮ ማኅበራዊ ተቋማት ሁሉ እየወደሙ ሲሆን፣ በተለይ ጋዛ ወደ ፍርስራሽነት ተቀይራለች፡፡
ከ42 ሺሕ የሚልቁ ዜጎችም ተገድለዋል፡፡ ነዋሪዎቿ ለሰብዓዊ ቀውስ ተዳርገዋል፡፡ ከሃማስና ሂዝቦላህ በኩል በእስራኤል የሚወሰዱ ዕርምጃዎች ሰላማዊ ተቋማት ላይ ያነጣጠሩ ናቸው ቢሉም፣ እስራኤል ዒላማዎቿ የቡድኖቹ መሸሸጊያ፣ የገንዘብና የጦር መሳሪያ ክምችት ያሉባቸውና ከቡድኑ ጋር ግንኙነት ያላቸው ናቸው ስትል ትገልጻለች፡፡ ከእስራኤል ወገንም ወታደሮችንና አዛዦችን ጨምሮ ከ1100 የሚልቁ ተገድለዋል፡፡
ከሃማስና ሂዝቦላህ የሚወነጨፉባትን ሮኬቶች በአብዛኛው ስትመክት የቆየችው እስራኤልም፣ ሂዝቦላህ በሰሜን እስራኤል የሰነዘረባትን ጥቃት ተከትላ በቴልአቪቭ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጇን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡
በፍልስጤም ከሚደርሱ ቁሳዊ ጉዳቶች በተጨማሪ ከጋዛ ሰዎች እንዲፈናቀሉና ሥፍራውን ለቀው መጠለያ እንዲገቡ እየተደረገ ይገኛል፡፡ የሚደረግላቸው ድጋፍም እየተስተጓጎለ ነው፡፡ በጋዛ ፍልስጤማውያን ከቀያቸው ሲሰደዱ፣ አይሁዶች በጋዛ መስፈር አለባቸው የሚሉ እስራኤላውያን ብቅ ማለት ጀምረዋል፡፡
ሲኤንኤን በጋዛ አይሁዶች እንዲሰፍሩ ጥሪ የቀረበበትን ዝግጅት አስመልክቶ እንደዘገበው፣ የእስራኤል ምክር ቤት አባላትን ጨምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ ቀኝ ዘመም የእስራኤል ወትዋቾች በጋዛ ድንበር አካባቢ በተዘጋጀ መድረክ በመኘት መንግሥት በጋዛ አይሁዶችን እንዲያሰፍር፣ ከጋዛ ፍልስጤማውያን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
እስራኤል ከሃማስ ጋር ጦርነት ከገጠመች ዓመት ቢሆንም፣ በሊባኖስ ሂዝቦላህ ላይ የከፈተችውን መጠነ ሰፊ ጥቃት የጀመረችው በቅርቡ ነው፡፡ ሆኖም በርካታ ዒላማዎችን መምታቷን እያስታወቀች ትገኛለች፡፡
ከሂዞቦላህ ጋር ግንኙነት አለው የተባለ ባንክን ጨምሮ ሆስፒታሎችና ሌሎች ተቋማት የአየር ጥቃት ሰለባ ሆነዋል፡፡ በሊባኖስ ጥቃት ከጀመረችበት ከመስከረም 2017 ዓ.ም. ማገባደጃ ወዲህም 3200 ዒላማዎችን መትቻለሁ ብላለች፡፡
ሂዝቦላህ በበኩሉ በእስራኤልና በወታደሮቿ ላይ 31 ጥቃቶችን መፈጸሙን፣ ለዚህም ሮኬቶች፣ ሚሳየሎችና ድሮኖች ጥቅም ላይ መዋላቸውን ጠቁሟል፡፡፡
የእስራኤል ጋዛ ፍልስጤም ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ ኢራን ሁለት ቀጥተኛ የሚሳይል ጥቃቶችን በእስራኤል ላይ ስትፈጽም፣ እስራኤልም በኢራን በውትድርና ተቋማት ላይ አንድ የአፀፋ ምላሽ ሰጥታለች፡፡ በቅርቡ ከኢራን ለተሰነዘረባት ጥቃት ምላሽ ለመስጠት ማቀዷም ተሰምቷል፡፡
በመካከለኛው ምሥራቅ ሰላም ይመጣ ዘንድ በእስራኤልና ፍልስጤም በኩል የሁለትዮሽ ስምምነት የሚደረግበት አካሄድ እንደሚያስፈልግ በተደጋጋሚ ተጠቅሶ፣ ሰላሙን ለማስፈን የመካከለኛው ምሥራቅና ምዕራባውያን የተሳተፉባቸው ውይይቶች፣ ቢደረጉም ለውጥ ሊያመጡ አልቻሉም፡፡
ኢራን በውክልና ከእስራኤል ጋር ታዋጋቸዋለች የሚባሉት ሃማስና ሂዝቦላህም ጥቃታቸውን እንደቀጠሉ ነው፡፡ እስራኤልም እነሱ ባሉበት ሁሉ ዕርምጃ ከመውሰድ አልቆጠብም ስትል አስታውቃለች፡፡
እስራኤል ውስጥ ከሚደርሱ ጥቃቶች ጀርባ አለች በመባል የምትወቀሰው ኢራን በበኩሏ፣ ለእስራኤል እንደማትተኛ እየገለጸች ነው፡፡ እስራኤል ከሃማስና ሂዝቦላህ ጋር የባችበት ጦርነት ወደ ኢራን ሊያመራ እንደሚችል ፍንጮች እየታዩ ነው፡፡
በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢራን ሚሽን በበኩሉ፣ እስራኤል ኢራን ላይ ለመውሰድ ላቀደችው ወታደራዊ ጥቃት አሜሪካ ዘመናዊ መሣሪያዎች በማቅረብ ጣልቃ እንዳትገባ አስጠንቅቋል፡፡
No comments yet. Be the first to leave a comment!
Silence Between the Lines
May 03, 2025
A Looming Hunger Crisis: Malnutrition Rises Amid Supply Disruptions in Ethiopia
April 26, 2025
Markets in Slump Ahead of Easter Celebrations
April 19, 2025
Reviving a Vanishing Tongue: The Return of Ge’ez
April 12, 2025
Ethiopia Reads: A Grassroots Revolution in Literacy
April 05, 2025
Trapped between poverty and peril: Ethiopia’s struggle to curb youth migration
March 29, 2025
Silenced by Techno-patriarchy
February 28, 2025
From Catcalling to Femicide: The Violence We’ve Learned to Survive
December 09, 2024
Ethiopia’s Fashion Stars Shine in Creative DNA: Ethiopia 2.0
December 03, 2024
Betrayed on Every Front: How the Law, Society, and Police Failed Tsega Belachew
November 19, 2024
New Education Bill Proposes No Student Ranking Until Grade 6: A Shift Towards Inclusive Learning
October 30, 2024
© Copyright 2025 Addis News. All rights reserved.