A

Addis

ዜና

October 30, 2024

‹‹በፕሪቶሪያው ስምምነት መሠረት የፈረሱት የትግራይ ክልል ምክር ቤትና የክልሉ ካቢኔ ብቻ ናቸው›› የመቀሌ ከተማ ምክር ቤት

Politic

By

ልዋም አታክልቲ

በፕሪቶሪያው ስምምነት የፈረሱት የትግራይ ክልል ምክር ቤትና የክልሉ ካቢኔ ብቻ በመሆናቸው፣ የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የመቀሌ ከንቲባን ከኃላፊነት የማንሳት ሥልጣን የለውም ሲል የመቀሌ ከተማ ምክር ቤት አስታወቀ።

የመቀሌ ከተማ ምክር ቤት አስተባባሪ ኮሚቴ ይህንን ያለው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ አዲሱን የመቀሌ ከንቲባ ረዳኢ በርኸን (ዶ/ር) ከሥራ ማገዳቸውን ተከትሎ ከሁለት ቀናት በፊት ባወጣው መግለጫ ነው፡፡

አቶ ጌታቸው ጥቅምት 15 ቀን 2017 ዓ.ም. በጻፉት ደብዳቤ አዲሱ ከንቲባ ረዳኢ በርኸ (ዶ/ር) ሕጋዊ ካልሆነው ተግባራቸው እንዲታቀቡና ምክር ቤቱን መጠቀሚያ በማድረግ የጊዜያዊ አስተዳደሩን ሥራ የሚጻረር ተግባር መፈጸም እንደማይችሉ ያሳሰቡ ሲሆን፣ በከተማዋ የሚገኙ የመንግሥት መዋቅሮችም ‹‹ሕገወጥ›› የተባሉት ከንቲባ የሚሰጧቸውን መመርያዎች ተቀብለው እንዳያስፈጽሙ አስጠንቅቀው ነበር፡፡

የማስጠንቀቂያ ደብዳቤውን ተከትሎ ሰፋ ያለ መግለጫ ያወጣው የመቀሌ ከተማ ምክር ቤት አስተባባሪ ኮሚቴ በበኩሉ የወረዳ፣ የከተማና የክፍለ ከተማ እንዲሁም የጣቢያ ምክር ቤቶች የሥራ ዘመን በክልሉ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 77(4) መሠረት አምስት ዓመት መሆኑን ገልጿል፡፡

ይሁን እንጂ በተሻሻለው የክልሉ ሕገ መንግሥት አዋጅ ቁጥር 105/1998 አንቀጽ ሁለተ፣ ንዑስ አንቀጽ (የ) መሠረት የወረዳ፣ የከተማ፣ የክፍለ ከተማና ጣቢያ ምክር ቤቶች የሥራ ዘመን ተጠናቆ አዲስ ምርጫ በማካሄድ ተተኪ ምክር ቤቶችን ለማቋቋም አዲስ ምርጫ ማካሄድ የማያስችል አስገዳጅ ሁኔታ መፈጠሩ ከታመነ፣ የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁት ምክር ቤቶች ከግማሽ የምርጫ ዘመን ላልበለጠ ተጨማሪ ጊዜ እንዲቆዩ ሊራዘምላቸው እንደሚችል መደንገጉንም አመልክቷል፡፡

ኮሚቴው ከላይ የተጠቀሱት መዋቅሮች አብያተ ምክር ቤት በ2006 ዓ.ም. መስከረም ወር የሥራ ዘመናቸውን ጀምረው በ2011 ዓ.ም. ምርጫ ማካሄድ ቢኖርባቸውም፣ በ2010 ዓ.ም. የኢሕአዴግ መንግሥት ተወግዶ የብልፅግና መንግሥት ወደ ሥልጣን ከመጣ በኋላ በአገር አቀፍ ደረጃ አስገዳጅ ለውጥ በመምጣቱ ምርጫ ማካሄድ አለመቻሉን አብራርቷል፡፡

በአገር አቀፍ ደረጃ የከተማ፣ ወረዳና ጣቢያ ምክር ቤቶች ምርጫ አለመካሄዱን ጠቅሶ፣ በ2013 ዓ.ም. ጥቅምት ወር ተቀስቅሶ ለሦስት ዓመታት በዘለቀው ጦርነት ምክንያትም ምርጫ ለማካሄድ የማያስችል አስገዳጅ ሁኔታ በመፈጠሩ በተሻሻለው የክልሉ ሕገ መንግሥት አዋጅ ቁጥር 105/1998 አንቀጽ 2 (የ) መሠረት፣ ምክር ቤቶቹ ሁለት ዓመት ከመንፈቅ የሥራ ዘመን ሊጨመርላቸው እንደሚገባ ገልጿል፡፡ በመሆኑም በተቀመጠው ድንጋጌ መሠረት በአቶ ጌታቸው ረዳ የሚመራው የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ለአዲሱ የመቀሌ ከንቲባ የጻፈው ደብዳቤ ተቀባይነት እንደሌለው አስታውቋል።

ከዚህም በተጨማሪ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የተቋቋመው የፌዴራል መንግሥት በወጣው ደንብ መሠረት ሲሆን፣ ይህ ደንብ ደግሞ መሠረት ያደረገው አዋጅ ቁጥር 359/1995 አንቀጽ 14 (ለ) እንደሆነ የጠቆመው መግለጫው፣ የተጠቀሰው አዋጅ አንቀጽ 14 (ለ) ድንጋጌ የክልል ምክር ቤቶችንና በዚህ የተቋቋመ ሥራ አስፈጻሚ ካቤኔን የፌዴራል መንግሥት ማገድ እንደሚችል ሥልጣን ይሰጣል እንጂ የወረዳ፣ የከተማ፣ የክፍለ ከተማና ጣቢያ ምክር ቤቶችን ለማገድ ሥልጣን እንዳልተሰጠው የመቀሌ ከተማ ምክር ቤት አስተባባሪ ኮሚቴ መግለጫ አስረድቷል።

‹‹የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ከላይ ከተገለጹት የክልሉ አስተዳደራዊ መዋቅሮች ጋር የምንሠራው ለሰላም ስንል እንጂ ሕጋዊ ሆነው አይደለም ማለቱ ተቀባይነትም ሆነ ሕጋዊ መሠረት የለውም፤›› በማለት፣ የመቀሌ ከተማ ምክር ቤት አስተባባሪ ኮሚቴ ወቅሷል።

በማከልም የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በአላስፈላጊ ጉዳዮች ከመጠመድ ይልቅ በሕጉ መሠረት በተሰጠው ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት የክልሉን ግዛታዊ አንድነት እንዲያስመልስ፣ ተፈናቃዮችን ወደ ቀዬአቸው እንዲመልስና የሕዝቡን ሰላምና ደኅንነት እንዲያረጋግጥ ጠይቋል፡፡

እያንዳንዱ አስተዳዳሪ የሚሾመውም ሆነ ከኃላፊነቱ የሚነሳው በምክር ቤቶቹ መሆኑን የጠቆመው ኮሚቴው፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ የምክር ቤቶቹን ነፃነት እንዲያከብርና የከንቲባው ተጠሪነት ለምክር ቤቱ በመሆኑ ጊዜያዊ አስተዳደሩ ይህንን ተረድቶ በሕጉ መሠረት እንዲሠራም አሳስቧል፡፡

በደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) የሚመራው ሕወሓት በጥቅምት ወር መጀመሪያ ባካሄደው ስብሰባ ረዳኢ በርኸ (ዶ/ር) የመቀሌ ከተማ ከንቲባ አድርጎ መሾሙ የሚታወስ ሲሆን፣ በአቶ ጌታቸው የሚመራው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በበኩሉ ጥቅምት 15 ቀን 2017 ዓ.ም. ባሠራጨው ደብዳቤ ከጊዜያዊ አስተዳደሩ ፈቃድና ዕውቅና ውጪ የሚደረግ ሹም ሽር  በጀት እስከ መገደብ የሚደርስ ቅጣት ሊያስጥል እንደሚችል አስጠንቅቋል፡፡

መንግሥታዊ ሥልጣንና ኃላፊነት የሌለው ‹‹ቡድን›› በማለት የተጠቀሰው በደብረ ጽዮን (ዶ/ር) የሚመራው ሕወሓት የሚያካሂዳቸውን ሕጋዊ ያልሆኑ ተግባራት እንዲያቆም፣ የጊዜያዊ አስተዳደሩን መመርያ በመቀበል ፍርድ ቤቶችን ጨምሮ የዞንና የወረዳ መዋቅሮች ሕጋዊ አሠራር መከተል እንዳለባቸውም አስገንዝቧል፡፡

ሕግ በሚጥሱ አካላት ላይ ሕጋዊ ዕርምጃ እንዲወስዱ፣ እንዲሁም በክልሉ በየመዋቅሩ ያሉ ምክር ቤቶች ጊዜያቸው ያለፈና ሕጋዊ መሠረታቸው ያበቃ መሆኑን በመቀበል ሹመት ከመስጠትና ከመሻር እንዲቆጠቡ ሲል አሳስቧል፡፡

አዲሱ የመቀሌ ከንቲባ ረዳኢ (ዶ/ር) ደብረ ጽዮን ገብረሚካኤል (ዶ/ር) በሚመሩት ሕወሓት ውስጥ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሆነው የተመረጡ ሲሆን፣ በጥቅምት ወር የመጀመሪያ ሳምንትም የቀድሞውን ከንቲባ አቶ ይትባረክ አምሐ በመተካት በከተማዋ ምክር ቤት ከንቲባ ሆነው መሾማቸው አይዘነጋም፡፡

Comments

No comments yet. Be the first to leave a comment!

Leave a Comment

Related Posts

Subscribe

You must accept the terms to subscribe.

© Copyright 2025 Addis News. All rights reserved.